የመሪዎች ሚና

በቀድሞው በሶሻሊዝም ዘመን ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ ነው ይባል ነበር ። ምንም እንኳን ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ መሆኑ ባይካድም የመሪዎች ሚና ዝቅ ተደርጎ ሊታይ አይችልም ። ለተወሰኑ አመታትም ቢሆን እንኳን ቢሆንም መሪዎች የአንድን ሀገር የታሪክ ሂደት አዝጋሚ ሊያደርጉ ወይንም የታሪኩን ሂደት አቅጣጫውን ሊያስቀይር ወይም ሊያስት የሚችል አቅም አላቸው ። በታሪክም አንደታየው ሀገራትን በመፍጠር ወይንም በመገንባት ወጽኝይንም በማፈራረስ መሪዎች ዋነኛ ተዋናንያን ናቸው ። ለምሳሌ ሀያሏን አሜሪካንን ብንወስድ ከእንግሊዝ ቅኝ አገዛዝ ነፃ ያወጧት ፣ ከዚያም አንድነቷን ጠብቀው ሌሎች ሀገሮች በዘውዳዊ ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ በሚገዙበት ዘመን በዲሞክራሲና በሪፐብሊክ እንድትተዳደር ያደረጉት በወቅቱ የነበሩት መሪዎቿ በወሰኑት ውሳኔ ነው ። መሪዎቹም ይህንን የወሰኑት በዘመኑ ምንም አስገዳጅ ነገር ኖሮባቸው ሳይሆን ይጠቅማል ብለው ባሰቡት መንገድ ነው ስለዚህ የመሪዎች ሚና በጣም ቁልፍ ነው ። 

የአንድ ሀገር መሪ ልክ እንደ በአውራ ጎዳና ውስጥ የሚጓዝ መኪናን እንደሚሾፍር ሹፌር ይመሰላል ። የመኪናዋ ልክ እንደ ሀገር ብትመሰል የመኪናው ሹፌር ደግሞ ልክ እንደ ገዢ ፓርቲ ወይም ሀገርን እያስተዳደረ እንዳለመሪ ቢመሰል ፣ ጎዳናው ሀገሪቱን ብሄራዊ ጥቅም አስከብራ የምትሄድበት ጎዳና ቢሆን ፤ የመኪናዋ መሪዎች መኪናዋ በምን ያህል ፍጥነት ፣ እንደምትሄድ መወሰን ይችላሉ ፣ ተበላሽታም ከሆነ ቆማ እንድትመረመር ፣ ወይም በምን ያህል ፍጥነት መሄድ እንዳለባት መወሰን ይችላሉ። በትክክል መንገዷን ጠብቃ ካልሄደችም ከመንገዷ የመውጣትና አደጋ ሊገጥማት ይችላል ።

      ሌላው ደግሞ መሪ ልክ መርከብን እንደሚመራ የመርከብ ካፒቴን ይመሰላል ።መርከቧ በየትኛው አቅጣጫ መሄድ እንዳለባት የሚወስነው ካፒቴኑ ሲሆን ረዳቶቹም የካፒቴኑን በማገዝ መርከቧ ወደ ሚፈለገው አቅጣጫ እንድትሄድ ያደርጋሉ ። ስለዚህ ሀገርም ልክ እንደ መርከቧ ብትመሰል ፣ መርከቧ በትክክለኛ አቅጣጫ ብትሄድ ልክ ሀገርም በትክክለኛ አቅጣጫ እንደመሄድ ማለት ነው ።

ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ ነው የሚል አባባል አለ ፣ ይሁን እንጂ የመሪዎችም ሚና ቀላል አይደለም ።የመሪዎች ተፈጥሯዊ ባህሪ ፣ አስተሳሰብ ሁሉ የራሱን በጎም ይሁን አሉታዊ ተፅእኖ ይኖረዋል ።በእርግጥ አንድ በሀገር ደረጃ የሚደረግ ነገርን የሚፈፅሙት ሰዎችና ማህበረሰቦች ስለሆኑ እነሱ ካልተሳተፉበት ያ ነገር እውን ሊሆን አይችልም ። ይሁን እንጂ መሪዎች በተወሰነ ደረጃ የአንድ ሀገርን ጉዞ ሊያፋጥኑ ወይም በተቃራኒው አቅጣጫ ከሄዱ ደግሞሊጎትቱት ይችላሉ ።

አንደ የመሪነት እሴቱ ትቶት የሚሄደው አሻራ ሲሆን ፣ አንድ መሪ በስልጣን የሚቆይበት ዘመን በጣም አጭር ሲሆን የትየለሌ ከሆነውና መጨረሻ ከሌለው ጊዜ አንፃር ስናየው ፣ እንኳን አንድ መሪ ስልጣን ላይ የሚቆይበት ቀርቶ የሰው ልጅ እድሜም የተገደበ ነው ። በጊዜ ውሱንነት በተገደበው የመሪው እድሜ ስናስበው ለረጅም ጊዜ ፀንቶ የሚቆይን ስራ መስራት መሪው ከህይወት በላይ የዘለቀ እንዲሆን ያደርገዋል ። መጽሀፉ የሰው ሁሉ እድሜ የተገደበ ነው እንደሚለው መሪም ሰው እንደመሆኑ እድሜውም ሆነ የስራ ዘመኑ በጊዜ ውስጥ የተወሰነና የተገደበ ነው ። ስኬታማ የሆኑና በብዙ ትውልዶች ተወዳጅ የሆኑ መሪዎች ይህንን ቀላል የሆነ ግን ብዙ ጊዜ ሰዎች ትልቅ ስልጣንንና ዝናን ሲቀዳጁ በቀላሉ የሚዘነጉት ሀቅ ነው ።

ብዙ ጊዜ የውጪ ጋዜጠኖች አንድ ተለቅ ያለ መሪን ቃለ – መጠይቅ ሲጠይቁ ብዙ ጊዜ የሚጠይቁት ጥያቄ ውስጥ ምን አይነት አሻራን ወይም ቅርስን ትተህ ማለፍ ትፈልጋለህ? በታሪክ ውስጥ እንዴት ለመታወስ ወይም ምን አይነት ቦታ እንዲኖርህ ትፈልጋለህ ? የሚል ነው ። ይሄም ውሎ አድሮ መሪው የሚሰራው ስራ ወደሚቀጥለው ትውልድ የሚተላለፍ ስለሆነ የወደፊቱ መጪው ትውልድ በምን አይነት እንዲያስተውሰውና ፣ ለመጪው ትውልድም ባለው ትልቅ ቦታና ተሰሚነት ምንን ትቶ ወይም አውርሶ ማለፍን እንደሚፈልግ ለማወቅ የሚደረግ ጥያቄ ነው ። በተዘዋዋሪም አሁን እየሰራው ያለው ስራ ለወደፊቱ የሚኖረውን በጎም ይሁን አሉታዊ ተፅእኖን መሪው እንዴት እንደሚረዳ ለማወቅ የሚደረግ ነው ።

ይህ ብቻ ሳይሆን መሪው ትቶት ሊያልፍ የሚፈልገው አሻራም አቅጣጫ ተቋሚ ይሆነዋል ። ሊተወው የሚፈልፈው ወይም ሊታወስበት የሚፈልገው ነገር ከዚያ በኋላ ለመሪው እንደ አቅጣጫ ጠቋሚ ሆኖ ሲያገለግለው ፣ ከዛ ጎዳና ላለመውጣት ይረዳዋል ።

የአንድ መሪ ስኬት የሚወሰነው በመሪው ችሎታ ብቻ ሳይሆን በሚመራው ተቋም እና በሚመራቸው ሰዎች ባህሪም ጭምር ሲሆን ጠንካራ ዲሲፕሊን ወይም ስነ-ስርአት ያለው ተቋም ለመሪው ስኬት ከፍተኛን አስተዋፅኦ ያደርጋል ።የዚህ አይነት ተቋማት በተቋም ደረጃ ከሌሎች በበለጠ ካሰቡት ግብ የመድረስ ወይም የመሳካት እድላቸው ከፍተኛ ነው ። የተለያዩ ክፍሎች ያሉት እንደሚያመለክተው ወታደራዊና ፖለቲካዊ ክፍል ቢኖረው ወታደራዊ ክፍሉ ለፖለቲካው ክፍል ታዛዥ መሆን ሲኖርበት ፣ ወታደራዊ ክፍሉ በሀይሉ ተመክቶ ለፖለቲካው ክፍል አልታዘዝም ቢል የመሪነት ውድቀት ነው እሚደርሰው ።

      መሪው ሊሳሳት ቢችልም ፣ መሪው ተሳስቷልና እሱን አንከተልም ቢሉና የመሪው ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዳይደረግ በውስጥ ለውስጥ ሴራ ወደ ሌላ አቅጣጫ ቢሄዱ ሊከተል የሚችለው የአመራርና የተቋም ውድቀት ቀላል አይሆንም። ግልፅነት ለመሪዎች አመራር አንዱ አስፈላጊ ሲሆን ግልፅ የሆነ አመራር ካለ የዜጎችም ሆነ የሰዎች መብት ሊሸራረፍ የሚችልበት እድል ይጠባል ።

አንዳንድ መሪዎች እነሱ እስካሉ ድረስ ነው እንጂ ከእነሱ በኋላ ስለሚመጣው ደንታ የማይኖራቸው ሲኖሩ በታሪክም በተደጋጋሚ ተመዝግቧል ። ወደ ሀገርኛው አባባል ስንመልሰው እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል አለች በአቅሎ ከሚለው አገርኛ አባባል ጋር ተነሳሳይ ነው ። ይሄ ነገር የግብፁ ፈርኦን በቀን በሺ የሚቆጠሩ በቅሎዎች ፣ በጎችና ፍየሎች የሚቀርቡለት የነበረ ቢሆንም እኔ ከእኔ በኋላ ግን ግንብፅን የአባይ ውሀ ይብላት ይል እንደነበረ በታሪክ ተመዝግቧል ።

ሀገራት ከሰዎች እድሜም ሆነ ጥንካሬ በላይ ያላቸው ናቸው ። ሀገርና ህዝብ ግን መሪዎች ቢቀያየሩም ፣ ብዙ ችግርንና ውጣ ውረዶች ቢያጋጥማቸውም ያንን ሁሉ ተቋቁመው መቀጠል ይችላሉ ። መሪነት ከስልጣን ጋር አብሮ ተያይዞ የሚገኝ ነገር ሲሆን ፤ ስልጣን ደግሞ የራሱ የሆነ የማይታለፍ መስመር ያለው ሲሆን ያ መስመር ከታለፈ ግን ስልጣንነቱ ያበቃል ። ስለዚህ በጣም ውጤታማ የሆኑ መሪዎች የዚህን መስመር ምንነት የተገነዘቡና ተግባራዊ የሚያደርጉ ናቸው ። ምንም እንኳን የዚህ አይነት መሪዎች ተወዳጅነታቸው የቀነሰ ቢሆንም ፤ ያንን ስልጣን ለምን አላማ ተጠቀሙበት የሚለው ነው ዋናው ቁም ነገር የሚሆነው ፤ ለግላቸው ስልጣን ግላዊ ለሆነ ጥቅም ካዋሉት የሚያስወቅሳቸው ብሎም ተጠያቂ የሚያደርጋቸው ሲሆን ፤ ለሚመሩት ተቋም ወይም ሀገር ስራ ላይ ካዋሉት ግን መጀመሪያ ባይወደዱበትም ውሎ አድሮ ግን ባመጡት ውጤት ሊመሰገኑ ይችላሉ ። በስልጣን ዘመናቸው በህዝብ ዘንድ ተወዳጅ (Popular) ያልነበሩ ነገር ግን ከስልጣን ከወረዱ ከብዙ ጊዜ በኋላ በታሪክ የሚመሰገኑ በርካታ መሪዎች ያሉ ሲሆን ፤ በአንፃሩ ደግሞ በዘመናቸው የተወደዱ  ነገር ግን ከስልጣን ከወረዱ በኋላ ስራቸው ብዙም ዘላቂ ያልሆነና ብዙም በበጎ የማይነሱ መሪዎች በአለማችን ላይ ተመላልሰዋል ።

Leave a comment