ፍትህና እውነት

እየሱስ ክርስቶስ ከሳሾቹ ጲላጦስ ፊት ባቀረቡት ወቅት ከጲላጦስ ጋር እንካ ሰላንታ በገጠመበት ወቅት ጲላጦስን «እውነት ምንድነች?» ብሎ ይጠይቀዋል ፣ በተመሳሳይም ታላቁ ፈላስፋ ሶቅራጥስ ተማሪዎቹን «ፍትህ ምንድን ነው?» ብሎ ይጠይቃቸዋል ። የእውነትና የፍትህ ጥያቄ በታሪክ ውስጥ በተደጋጋሚ የተከሰተና ቁልጭ ያለ መልስ ያላገኘ ነው ።

ንግድ ፍትህን ያሰፍናል ብለን ብናስብ ፣ አን ራንድ እንደምትለው «በሰዎች መሐከል በጣም ፍትሀዊ የሆነው ግንኙነት ንግድ ነው» ትላለች ። ንግድ የራሱ ስርአት ያለው ሲሆን ፣ በአለም የንግድ ስርአት ውስጥ የአለም የንገድ ስርአት ፍትሀዊ አለመሆኑ የተገለፀ ጉዳይ ስለሆነ ምንም እንኳን ሁለት ሐገራት ቢነግዱም ያ የንግዳቸው ስርአት ፍትሀዊ ነው ማለት አይቻልም ። ንግድ የራሱ ስርአት ፣ ደንብና አካሄድ ያለው ነገር ሲሆን ንግዱ በምን መንገድ መካሄድ እንዳለበት የሚወስነው አካል በንግዱ ሂደት ውስጥ የበላይነቱን ለራሱ ማስፈን ይችላል ። ስለዚህ በአንድ ደሀ ፣ በግብርና የሚተዳደር አገርና አንድ በኢንዱስትሪ የበለፀገ አገር እኩል እና ፍትሀዊ የሆነ የንግድ ስርአት በመሀከላቸው መኖረና መፈጠር መቻሉ  እጅግ አጠራጣሪ ነው ።

ለምሳሌ አንድ ሀብታምና አንድ ደሀ እርስ በእርሳቸው ቢነግዱ ሀብታሙ ለደሀው ጉልበቱን ቢገዛው ፣ ደሀው ጉልበቱን ለመሸጥ አማራጭ ስለሌለው ለሀብታሙ በሰጠው ዋጋ የመሸጥ ግዴታ ሊኖርበት ይችላል ። በአንፃሩ ሀብታሙ አማራጭ ስላለው  በገንዘቡ የፈለገውን የማሰራት አማራጭ አለው ። ደሀው አማራጩ ጠባብ ስለሚሆን ያለው አማራጭ ሀብታሙ በሰጠው ዋጋ ጉልበቱን መሸጥ ሊሆን ይችላል ።   

በአለም ላይም እንዲሁ በሀብታም በኢንዱስትሪ በበለፀጉና በደሀ ሀገራት መሀከል የሚደረግ የንግድ ግንኙነት ፍትሀዊ አለመሆኑ የታወቀ ነው ። አንድ በኢንዱስትሪዎቹ አማካይነት ያለማቋረጥ ሰራተኞችን እየቀያየረ በፋብሪካዎቹ ማምረት የሚችል ሀገርና ፣ አንድ በግብርና የሚተዳደር ሀገር እኩል ሊነግዱ አይችሉም ።  

Leave a comment